1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ በተከሰተ ግጭት የሰው ህይወት አለፈ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 6 2016

ከትናንት በስቲያ እሁድ አንስቶም በወረዳው በተከሰቱ ግጭቶች ሠላማዊ ሰዎች ህይወት ማለፉንም ገልጸዋል፡፡ እሁድ በወረዳው ውስጥ በተከሰተው ግጭት 10 ሰዎች ህይወት ማለፉን እና 17 የሚደርሱ ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ተናግረዋል፡

https://p.dw.com/p/4fqF1
የጋምቤላ ክልል ርዕሰ ከተማ ግምቤላ አደባባዮች አንዱ
የጋምቤላ ክልል ርዕሰ ከተማ ግምቤላ አደባባዮች አንዱ ምስል Negassa Desalegn/DW

በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ በተከሰተ ግጭት የሰው ህይወት አለፈ

በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ ውስጥ ባለፈው ዕሁድና ትናንት በተከሰተው ግጭት የጸጥታ ሐይሎችን ጨምሮ  በትንሹ የ9 ሰዎች  ተገደሉ፡፡ አንድ የአካባቢው ነዋሪ የ10 ሰዎች ህይወት ማለፉን የተናገሩ ሲሆን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ደግሞ 9 ሰዎች መሞታቸውን አመልክተዋል፡፡በወረዳው አንድ ቀበሌ ውስጥ ታጣቂዎች ጥቃት በመክፈታቸዉ ከጸጥታ ሀይሎች ጋር ግጭት መከሰቱ ተነግሯል፡፡ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽነር ኡሞድ ኡሞድ እንደተናሩት በተኩስ ልዉዉጡ 6 ንጹሐን  ዜጎችና ሶስት የጸጥታ ሀይሎች ተገድለዋል፡፡አንድ ነዋሪ ግን በአካባቢው የሚገኙ የኑዌር ብሔረሰብ አባላት ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ደርሷል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በግጭቱ የጸጥታ ሐይሎችን ጨምሮ 9 ሰዎች ተገድለዋል

 ከጋምቤላ ከተማ በ46 ኪ.ሜ ርቀት ገደማ ላይ በሚትገኘው ኢታንግ ልዩ ወረዳ የኑዌርና አኙዋክ ብሔረሰቦች በብዛት ይኖራሉ፡፡ በዚህ ወረዳ ከሚያዚያ 29/2016 ዓ.ም ወዲህ ተደጋጋሚ ጥቃት መድረሳቸውን ያነጋገርናቸው አንድ ነዋሪ አመልክተዋል፡፡ ከትናንት በስቲያ እሁድ አንስቶም  በወረዳው በተከሰቱ ግጭቶች ሠላማዊ ሰዎች ህይወት ማለፉንም ገልጸዋል፡፡ እሁድ በወረዳው ውስጥ በተከሰተው  ግጭት 10 ሰዎች ህይወት ማለፉን እና 17 የሚደርሱ ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ተናግረዋል፡፡ ግጭቱ ጸጥታ ሀይሎች ጋር በተፈጠረው አለመግባባት የተከሰተው እንደሆነ ነዋሪው ተናግረዋል፡፡ ማኮትና ሌሪ በሚባሉ የወረዳው ቀበሌዎች ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ማንነት ተኮር ጥቃቶች ይደርሱ እንደነበር ነዋሪው አክለዋል፡፡

የጋምቤላ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ኡሞድ ኡሞድ በኢታንግ ልዩ ወረዳ የተከሰተው የሠላም መደፍረስ አስመልክቶ በሰጡን ማብራሪያ በአካባቢው ህገ ወጥ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ግለሰቦች የፈጠሩት ችግር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ የጸጥታ ሐይል በስራ ላይ ተሰማርቶ ባለበት ሰዓት ጥቃት እንዳደረሱበት አመልክተዋል፡፡ ግለሰቦቹ መሳሪያቸውን ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆን በጸጥታ ሀይሎች ላይ ተኩስ መክፈታቸውንና ሌሎች ጥቃቶችን አድርሰዋል ብሏል፡፡ በደረሰው ጥቃት ጸጥታ ሐይሎችን ጨምሮ 9 ሰዎች ህይወት ማለፉን አብራርተዋል፡፡ ወደ ኢታንግ ልዩ ወረዳ በእጀባ ይሰጥ የነበረው የትራንስፖርት አገልግሎት ለ2 ቀን ተቋርጦ እንደቆየ ገልጸው በዛሬው ዕለት ደግሞ አንጻራዊ የጸጥታ መረጋጋት እንዳለ ጠቁመዋል፡፡

በኢንታንግ ልዩ ወረዳ ሰሞኑን የተደረገዉ ግጭት ከዚሕ ቀደም ከሚደረጉ ግጭቶች ጋር የተያያዘ እንደሆነ ነዋሪዎች ይናገራሉ
ጋምቤላ ዉስጥ በተለያዩ አካባቢዎች በተደጋጋሚ በሚደረግ ግጭት የሰዉ ህይወት ይጠፋል ንብረትም ይወድማልምስል Anywaa Survival Organisation/Nyikaw Ochalla

በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ በተለያዩ ወቅቶችበሚከሰቱ ግጭቶች ለበርካታ ሰው ህይወት ማለፍና ንብረት ውድመት ምክንያት እየሆነ እንደሚገኝ ነዋሪዎች  ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ሰሞኑን በኢታንግ ልዩ ወረዳ የደረሰውን ጉዳት አስመልክቶ 3 ጥቆማዎች እንደደረሱትና መረጃ በማሰባሰብ ላይ እንዲገኝ ጠቁመዋል፡፡ ኮሚሽኑ በየካቲት ወር ውስጥ ባወጣው የምርመራ ሪፖርት ከግንቦት 2015 ዓ.ም ጀምሮ  በኢታንግ ልዩ ወረዳ ሌሎች የክልሉ አካባቢዎች የተከሰቱ ግጭቶት በመቶዎች ለሚቆጠር ህይወት ማለፉንና ንብረት መውደሙን መግለጹ ይታወሳል፡፡ በቀጣይ ተመሳሳይ ችግሮች እንዳይከሰቱ ጥፋተኞች ተጠያቂ እንዲሆኑ፣ተጎጂዎችም እንዲካሱ በማድረግ የተሟላ ፍትህ ማረጋገጥ እንደሚጠበቅ ኮሚሽኑ በወቅቱ ጠቁሟል፡፡

ነጋሳ ደሳለኝ

ነጋሽ መሐመድ

ታምራት ዲንሳ